አዋሽ ባንክ በ2019/20 የሂሳብ ዓመት ከፍተኛ ትርፍ አስመዝግቧል፡፡

የአዋሽ ባንክ የባለአክሲዮኖች 25ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ህዳር 19 ቀን 2013 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሒልተን ሆቴል ተካሂዷል፡፡ የኮሮና ቫይረስ በአለም አቀፍ ደረጃ የኢኮኖሚ ቀውስ እያስከተለ ቢሆንም አዋሽ ባንክ በአስር ዓመቱ ፍኖተ ካርታው ላይ ባስቀመጠው ስትራቴጂ በመመራትና ሊያጋጥሙ የሚችሉ ቀውሶችን ለመቆጣጠር የሚያስችሉትን ስትራቴጂዎችን በመተግበር የበጀት ዓመቱን በአመርቂ ውጤት ማጠናቀቁን የአዋሽ ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አምባሳደር ዶ/ር ዲባባ አብደታ ለጠቅላላ ጉባኤው ገልፀዋል፡፡

ያለፈው በጀት ዓመት በዓለማችን ከተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ የተነሳ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ በአጠቃላይና ለባንኪንግ ኢንዱስትሪው ደግሞ በተለየ ሁኔታ ፈታኝ ከመሆኑም በተጨማሪ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የሚሄደው የዋጋ ንረት፣በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የነበሩ የፖለቲካ አለመረጋጋቶችና የፀጥታ ስጋት፣በባንኮች መካከል ያለው ከፍተኛ ፉክክር እያደገ የመጣበት ዓመት  የነበረ  ቢሆንም ባንካችን ያስመዘገበው አኩሪ ውጤት ከቀደሙት ዓመታት እጅጉን የላቀ እንደነበር የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢው ገልፀዋል፡፡

አዋሽ ባንክ በየጊዜው የሚያስመዘግባቸው ተከታታይ ዕድገቶች ባንኩን በጠንካራና አስተማማኝ መሠረት ላይ እያቆሙት መሆኑን የቦርድ ሰብሳቢው ጠቁመዋል፡፡

ይህ አመርቂ ውጤት ሊገኝ የቻለው የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድና የስራ አመራር አባላት ተቀናጅቶ መስራትና በየደረጃው ያሉ የባንኩ ሠራተኞች ባሳዩት ከፍተኛ የስራ ተነሳሽነትና ቁርጠኝነት ነው ያሉት አምባሳደር ዶክተር ዲባባ አብደታ፣ለዚህም የበኩላቸውን አስተወፅኦ ላበረከቱ ባለድርሻ አካላት ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

የአዋሽ ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ፀሐይ ሽፈራው በበኩላቸው 2019/20 የሂሳብ ዓመት አዋሽ ባንክ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በአገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ለመቀነስና ለመቋቋም መንግስት ለሚያደርገው ጥረት ተገቢውን ድጋፍ በማድረግ ህዝባዊነቱን ያስመሰከረበት ዓመት ከመሆኑም ባሻገር ባስመዘገበው ዓመታዊ ትርፍም ለአምስተኛ ጊዜ መሪነቱን አረጋግጧል ብለዋል፡፡

ባንኩ ወረርሽኙ ቀጥተኛ ተፅዕኖ ላሳረፈባቸው በተለይ የሆቴል፣ የአበባና አስጎብኚ ድርጅቶች የተለያዩ እፎይታዎችን በማድረግ ቢዝነሳቸው ለከፋ ችግር እንዳይጋለጥ ለማድረግ ተችሏል፡፡ የባንኩ ደንበኞችና ሰራተኞችን ከወረርሽኙ ለመከላከልም በሚሊዮኖች የሚገመት ገንዘብ በማፍሰስ የተለያዩ የመከላከያ ግብዓቶችን የማቅረብና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ሰርቷል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃም ለመንግስትና መንግስታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ድጋፍ በማድረግ ለወረርሽኙ ሰለባዎች ሰብዓዊ ዕርዳታ እንዲደርስ ማድረጉንም አቶ ፀሐይ አስረድተዋል፡፡

አዋሽ ባንክ በ2019/20 የሒሳብ ዓመት ማጠናቀቂያ ላይ:-

  • በተቀማጭ ገንዘብ የ19 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ ብር 74.3 ቢሊዮን ደርሷል፡፡
  • በብድር የ21 በመቶ ዕድገት ባመስመዝገብ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የተሰጠው ብድር ብር 57.3 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ የባንኩ የተበላሸ ብድር ምጣኔ  በበጀት ዓመት ማጠቃለያ ላይ 1.7 በመቶ ነበር፡፡ ይህ ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው የአምስት በመቶ ምጣኔ አንፃር ሲታይ እጅግ መልካም የሆነ አፈፃፀም ሲሆን የባንኩ ብድርም ጠነኛ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡
  • በበጀት ዓመቱ ማጠቃለያ የባንኩ አጠቃላይ የሀብት መጠን የ19.7 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ ብር 89.3 ቢሊዮን የደረሰ ሲሆን፣
  • የባንኩ ካፒታል ደግሞ እ.ኤ.ኤ. ሰኔ 30 ቀን  2019 ከነበረበት ብር 4.38 ቢሊዮን የብር 1.46 ቢሊዮን ወይም የ33.4 በመቶ ዕድገት በማሳየት እ.ኤ.አ ሰኔ 30 ቀን 2020  መጨረሻ ላይ ብር 5.85 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ በሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ የባንኩ የተከፈለ ካፒታል ብር 12 ቢሊዮን እንደሚደርስ ተጠቁሟል፡፡
  • በአጠቃላይ የትርፍ መጠን የስምንት በመቶ ዕድገት በማሳየት የብር 3.6 ቢሊዮን ዓመታዊ ትርፍ ማስመዝገቡንም ገልፀዋል፡፡

በሌላ መልኩ  በ2019/20 የሒሳብ ዓመት አዋሽ ባንክ፡-

  • በጅማ ከተማ ባለ ስድስት ወለል ህንፃ በማስመረቅ ለአገልግሎት አብቅቷል፤ በአዲስ አበባ የቡልቡላ ቅርንጫፍ እና በባሌ ሮቤም የአዳዲስ ህንፃዎች ግንባታ አስጀምሯል፡፡
  • የባንኩን ሰራተኞች አቅም ለመገንባት ሲባል በባንኩ የስልጠና ክፍል፣ በአገር ውስጥና ከአገር ወጪም ስልጠናዎችን በተሳካ ሁኔታ ሰጥቷል፡፡
  • በበጀት ዓመቱ ከ1.3 ቢሊዮን ብር በላይ ግብር በመክፈል የዓመቱ ታማኝና ከፍተኛ ግብር ከፋይ በመባል በፕላቲኒየም ደረጃ በኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) የዕውቅና ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡

Share
Facebook
Twitter
LinkedIn
Telegram

Nov 28, 2023 EXCHANGE Rate
Currency Buying Selling
USD
55.6854 56.7991
GBP
67.1870 68.5307
EUR
60.9588 62.1780
AED
13.7216 13.9960
SAR
13.4363 13.7050
CHF
60.3764 61.5839

Exchange Rate
Close