አዋሽ ባንክ የ2018 ዓ.ም የገና በዓልን ምክንያት በማድረግ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ውስጥ ለሚገኙ አረጋዊያን እና አቅመ-ደካማ ወገኖች የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ አደረገ። ባንኩ በዘንድሮ የገና በዓል “ክብራችን ወገናችን – ደስታችን ማካፈላችን” በሚል መሪ ቃል ለወገኖቻችን ድጋፍ በማድረግ ህዝባዊ ወገንተኝነቱን ዳግም ያረጋገጠ ሲሆን፣ በዛሬው እለትም የአዋሽ ባንክ ሲኒየር ቺፍ ማርኬቲንግ ኦፊሰር አቶ ዮሐንስ መርጋ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች በመላው ሀገሪቱ ባንኩ የሚያደርገውን የአይነትና የገንዘብ ድጋፍ በሰዓሊተ ምህረት ቤተክርስቲያን በመገኘት መረሃ ግብሩን አስጀምረዋል፡፡
ባንኩ ላለፉት ዓመታት ታላላቅ ህዝባዊና ኃይማኖታዊ በዓላትን ምክንያት በማድረግ ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች ዘርፈ ብዙ ድጋፎችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የ2018 የገና በዓልን ምክንያት በማድረግ አዲስ አበባን ጨምሮ በመላው ኢትዮጵያ በተለያዩ 50 የድጋፍ መስጫ ጣቢያዎች የድጋፍ መርሃ-ግብር በማካሄድ ላይ ይገኛል። በዚህ የድጋፍ መርሃ-ግብር ጠቅላላ ግምቱ በነፍስ ወከፍ ከብር 9ሺህ በላይ የሆነ የ5ሊትር ዘይት፣25ኪሎ ዱቄትና የ3ሺህ ብር ጥሬ ገንዘብ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል።
ከዚህ ጋር ተያይዞ ”ክብራችን ወገናችን – ደስታችን ማካፈላችን” በሚል መልዕክት ከአምስት ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወገኖች እየተደረገ ባለው የበዓል መዋያ የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ ባንኩ ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጓል። ባንኩ በቀጣይም መሰል ድጋፎችን አጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል፡፡



















